2018-01-20 17:40:00

ር. ሊ. ጳ. ፍራንቸስኮ በፔሩ በአማዞን ደን አከባቢ ከሚኖሩ ሕዝቦች ጋር ተገኝተው ተመያዩ።


ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ፣ ሃያ ሁለተኛቸው የሆነውን ሐዋርያዊ ጉብኝት ለማድረግ፣ የላቲን አሜሪካ አገሮች ወደ ሆኑት ወደ ቺሊና ወደ ፔሩ መጓዛቸው ይታወቃል። የቺሊ ጉብኝታቸውን ከፈጸሙ በኋላ ወደ ፔሩ ሄደው በዚያም ሐዋርያዊ ጉብኝታቸውን በማድረግ ላይ ይገኛሉ።

በፔሩ በሚገኘውና ስፋት ባለው በአማዞን ደን ውስጥ የሚገኘውን ሕዝብ ጎብኝተዋል። ወደ አካባቢው ሲሄዱ የመጀመሪያው ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ናቸው ተብሏል። ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በተያዘላቸው ቀጠሮ መሠረት በሥፍራው በመገኘት ከአካባቢው ሕዝብና ተወካዮች ጋር በመገናኘት ንግግርም አድርገውላቸዋል። ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ለአማዞን ሕዝብ ያደረጉትን ንግግር ተርጉመን እንደሚከተለው አቅርበነዋል።         

የተወደዳችሁ ወንድሞቼና እህቶቼ፣

በዚህ ሥፍራ ከእናንተ ጋር በመሆን፣ ከልቤ የሚፈልቀውንና “ዉዳሴ ላንተ ይሁን” የሚለውን የቅዱስ ፍራንችስኮስ መዝሙር አብረን እንዘምራለን። ሁላችን ወደዚህ ሥፍራ ምጥተን እንድንገናኝ ስለፈቀድከን ውዳሴ ላንተ ይሁን። የአጊረ ጊነኣ ጳጳስ የሆኑትን ሞንስኞር ዳቪድ ማርቲነዝን፣ አቶ ሄክቶርን፣ ወይዘሮ የሲካንና ወይዘሮ ማርያ ሉዝሚላን፣ ለመልካም አቀባበል ንግግራችሁና ለምስክርነታችሁ አመሰግናችኋለሁ። በእናንተም አማካይነት ለመላው የአማዞን ነዋሪዎች የከበረ ሰላምታዬን ከምስጋና ጋር ማቅረብ እወዳለሁ።

በአማዞንያ ከሚገኙ በርካታ አውራጃዎች እንደመጣችሁ እረዳለሁ። ይህን ሐዋርያዊ ጉብኝት ለማድረግ ብዙ ተምኝቼ አለሁ። በፔሩ የማደርገውን ሐዋርያዊ ጉብኝቴን ከዚህ ለመጀመር ፈልጌአለሁ። በቁጥር በርከት ብላችሁ ሳያችሁ፣ መልካችሁንም በቅርበት በማየት አገራችሁንም እንዳውቅ ስላደረጋችሁኝ አመሰግናልሁ።             

የብዛታችሁን ያህል፣ በርካታ ባሕላዊና መንፈሳዊ ሃብት አላችሁ። ለረጅም አመታት ያካበታችሁት እውቀትና ጥበብ፣ አካባቢያችሁን በሚገባ ሳናውቅ ለምንመጣ፣ በተፈጥሮ ላይ ጉዳትን እንዳናደርስ መልካም ትምህርት ይሆነናል። (“ወደዚህ እንዳትቀርብ፣ ይህች የቆምክባት ምድር የተቀደሰች ስለሆነች ጫማህን አውልቅ።ዘጸዓት ምዕ 3 5)

የአማዞን መሬት ለያዘው ሰፊ የተፈጥሮ ሃብት እና ሕዝቦች እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ። ከአመታት ወዲህ የአማዞን ሕዝብ ሸክም ከባድ እየሆነ መምጣቱ የሚታይ ነው። ወደዚህ ሥፍራ እንድመጣ ከገፋፉኝ ምክንያቶች አንዱም ይህ ስለሆነ ሸክማችሁን ለመጋራት፣ ችግራችሁን በማዳመጥ፣ በአካባቢያችሁ፣ በሕይወታችሁና በባሕላችሁ ላይ የሚመጣውን ጥቃት ከመላዋ ቤተክስቲያን ጋር ሆነን ለመመከት ያለኝን ልባዊ ፍላጎቴን ላረጋግጥላችሁ እወዳለሁ።

በአማዞን ሕዝብ ታሪክ ውስጥ፣ ሕዝቡ የዛሬን ያህል የከፋ ጊዜ ገጥሞት አያውቅም። የአማዞን ግዛት በተለያዩ አቅጣጫዎች ጥቃት እየደረሰበት እንደሆነ ይስተዋላል።

የአማዞን መሬት የያዘውን በርካታ የተፈጥሮ ሃብት ነዳጅ፣ የተፈጥሮ ጋዝ፣ ወርቅ እና ዛፎችም ላይ ብዙዎች እጃቸውን አስገብተዋል። የቦታውን ሕዝቦች ሕይወት ያላገናዘበ የመንግሥት የተፈጥሮ ጥበቃ ፖሊሲዎች በነዋሪው ላይ ችግር እያስከተለ ይገኛል።

ስለዚህ በቅድሚያ ለአካባቢው ነዋሪ ለሆነው ሕዝብ ትኩረት በመስጠት ለባሕሉ፣ ለቋንቋው፣ ለመብቱና ለሐይማኖታዊ እሴቶች አስፈላጊውን ክብር መስጠት ያስፈልጋል። ለረጅም ዓመታት ሕዝቡ ተከፋፍሎ እንዲኖር ምክንያት የሆነውን የእርስ በርስ ውይይት አለመኖርን መልሰን በማምጣት መተዋወቅን፣ የቅርብ ግንኙነቶችን ማጠናከር ያስፈልጋል። ይህም በማንነታችሁና በይዞታቸሁ የሚመጣውን አደጋ በሕብረት ሆኖ ለመከላከል ይጠቅማል።

ሕብረታችሁን ማጠናከር፣ በአካባቢያችሁ የሚገኘውን የተፈጥሮ ሃብት በሚገባ ለመጠቀም ከእናንተ መካከል የሚመነጩ ሃሳቦችን በማስተባበር የተሻለ ኑሮን መኖር እንድትችሉ ያደርጋል። መሬታችንን መጠበቅ ወይም መከላከል ማለት መላ ፍጥረትን መንከባከብ ማለት ነው። በአየር ብክለት ምክንያት የበርካታ ቤተሰብ ጤና ችግር ውስጥ ወድቋል። በተመሳሳይ መልኩ በሕገ ወጥ የማዕድን ቁፋሮ ምክንያት በርካታ ቤተሰብ ለጤና መቃወክ፣ ለባርነት፣ ለጾታ ጥቃት ተዳርገዋል። ሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውርም በመስፋፋቱ የዚህ ሰለባ የሆኑትን ሳስብ ሐዘን ይሰማኛል። እንዲህ የሚለውን የእግዚ አብሔር ቃል ማዳመጥ ብንችል መልካም ነው። (“ወንድምህ የት አለ?” ዘፍጥረት ምዕ 4 9) በባርነት የተሸጡ ወንድሞቻችንና እህቶቻችን ባሁኑ ጊዜ የት ይገኛሉ ብለን ራሳችንን መጠየቅ ያስፈልጋል።  

በቅዱስ ቱሪቢውስ የደረሰውን በደል በማስመልከት ሦስተኛው የሊማ ምክር ቤት ያወጣውን መግለጫ ማስታወስ እንዴት ያቅተናል? በጥንት ዘመን በደካሞች እና በድሆች ላይ የሚደርሰው በደል አሁን በዘመናችንም እየደረሰ ይገኛል በማለት በአማዞን ደን ውስጥ የሚኖሩ ደሃ ማሕበረሰብ ላይ፣ በሚኖሩበት አካባቢ ተፈጥሮአዊ ሃብቶች ላይ፣ በባሕላቸው ላይ፣ በእምነታቸው ላይ፣ በመብታቸውም ላይ እየደረሰ ያለውን በደል በጋራ በመሆን መከላከል እንድሚያስፈልግ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ሰፋ ባለ ንግግራቸው አሳስበዋል። 








All the contents on this site are copyrighted ©.