2018-05-12 13:19:00

የመቁጠሪያዋ የፋጢማ ማሪያም የተገለጸችበት መቶኛው አመት በነገው እለት በግንቦት 05/2010 ዓ.ም በደመቀ ሁኔታ ይከበራል


የመቁጠሪያዋ የፋጢማ ማሪያም የተገለጸችበት መቶኛው አመት በነገው እለት በግንቦት 05/2010 . በደመቀ ሁኔታ ይከበራል

ይህ አሁን የምንገኝበት ወር የግንቦት ወር እንደ ሆነ ይታወቃል። ይህ የግንቦት ወር በወር ደረጃ በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ምዕመናን ዘንድ የማሪያም ወር በመባል የሚታወቅ ሲሆን በእዚህም የግንቦት ወር ውስጥ የክርስቶስ፣ የቤተክርስቲያን፣ የምዕመናን እናት ለሆነችው የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም ለየት ባለ መልኩ ጸሎት የሚደርግበት፣ አማልጅነቷን የምንማጸንበት፣ በተለይም ደግሞ በውስጣችን፣ በቤተሰባችን፣ በማኅበረሳባችን፣ በሀገራችን እና በአጠቃላይ በዓለም ውስጥ የጥል እና የክርክር ግድግዳ ተደርምሶ በአንጻሩ የሰላም እና የብልጽግና መንፈስ ይወርድ ዘንድ በእርሷ አማካይነት ወደ ልጇ ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመማጸኛ ጸሎት እንድታቀርብልን እርሷን በተለየ ሁኔታ በመቁጠሪያ ጸሎት አማልጅነቷን የምንማጸንበት ወር ነው የግንቦት ወር።

የእዚህን ዝግጅት ሙሉ ይዘት ከእዚህ በታች ያለውን ተጫወት የሚለውን ምልክት በመጫን ማዳመጥ ትችላላችሁ!

ይህ የያዝነው የግንቦት ወር ለእናታችን ለቅድስት ማሪያም ለየት ባለ ሁኔታ ጸሎት የምናቀርብበት ወር እንደሆነ የሚታወቅ ሲሆን በተለይም እንደ ጎርጎሮሳዊያኑ የቀን አቆጣጠር በግንቦት በ1917 ዓ.ም የዛሬ አንድ መቶ ዓመት ገደማ ማለት ነው በፖርቹጋል ሀገር ፋጢማ በሚባል መንደር ውስጥ ይኖሩ ለነበሩ ሦስት እረኛ ሕጻናት የመቁጠሪያዋ እናታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም የተገለጠችበት ቀን መቶኛ አመቱ በነገው እለት ማለትም በግንቦት 05/2010 ዓ.ም በመላው የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ምዕመናን ዘንድ በደመቀ ሁኔታ ይከበራል።

በወቅቱ እረኞች ለነበሩ ሦስት ሕፃናት እንደ ጎርጎሮሳዊያኑ የቀን አቆጣጠር የዛሬ 100 ዓመት ገደማ 1917 ዓ.ም. በፖርቱጋል ሀገር በሚገኘው ፋጢማ በሚባለው አከባቢ ልዩ ስሙ ኮቫ ዳ ኢራ በተባለው ሥፍራ ለሦስት ታዳጊ የከብት ጠባቂ እረኞች ለነበሩ ሕፃናት ፍራሲሽኮ፣ ዣሺንታ ማርቶ እና ሉሲያ ለተባሉ ሦስት ታዳጊ ለነበሩ ልጆች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያ የተገለጸችላቸው መሆኑ የሚታወቅ ሲሆን በወቅቱ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት የነበሩት ፒዮስ ሰባተኛ እንደ ጎርጎሮሳዊያኑ የቀን አቆጣጠር በግንቦት 13/1946 ዓ.ም. የእዚህን ግልጸት ትክክለኛነት ከመረመሩ ቡኃላ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም ሥም የንግደት ሥፍራ ይሆን ዘንድ ቤተ መቅደስ እንዲሠራ ፈቃድ መስጠታቸውና እስከ ዛሬም ድረስ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ምዕመናን በሥፍራው ንግደት በማድረግ እንደ ሚገኙም ይታወቃል።

በወቅቱ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም ለእነዚህ 3 ሕፃናት በመገለጽ ከጥቂት ዓመታት ቡኃላ ሁለተኛ የዓለም ጦርነት እንደ ሚነሣ በመተንበይ ሁሉም ክርስቲያኖች ሰላም ይሰፍን ዘንድ በእየለቱ የእመቤታችንን የቅድስት ድንግል ማሪያም የመቁጠሪያ ጸሎት እንዲያደርጉ ከእመቤታችን ትዕዛዝ መቀበላቸው ይታወቃል።

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም ለ3 እረኛ ለነበሩ ሕጻናት እንደ አውሮፓዊያኑ የቀን አቆጣጠር በግንቦት 13/1917 ዓ.ም. ለመጀመሪያ ጊዜ ተገልጻ እንደ ነበረ ቀደም ሲል መግለጻችን የሚታወስ ሲሆን የመቁጠሪያይቱ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም በቀዳሚነት የተገለጸችው ለሐብታም፣ ለባለስልጣናት ወይም ደግሞ ተጽኖ ፈጣሪ ለሆኑ ሰዎች ሳይሆን ነገር ግን በወቅቱ በማሕበረሰቡ የተናቀ ስፍራ ለነበራቸው እና በእረኝነት ለሚተዳደሩ ሕጻናት ነበር።

ፋጢማ በሚባል ልዩ ስፍራ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም ለእነዚህ 3 ሕጻናት እረኞች የተገለጸችበት ወቅት ዓለማችን በመጀመሪያው የዓለም ጦርነት እየታመሰች በምትገኝበት ወቅት እንደ ነበረ ይታወሳል።  በወቅቱ የነበረው የጥላቻ፣ የክህደት፣ የጠላትነት ስሜት በከፍተኛ ደረጃ ይታይ ነበር። የቀድሞ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ሊቃነ ጳጳሳት የነበሩት በበኔዴክቶስ 16ኛ እንደ የውሮፓዊያን የቀን አቆጣጠር በግንቦት 13/2010 ዓ.ም. ይህንን የመቁጠሪያዋ ቅድስት ድንግል ማሪያምን ቤተ መቅደስ በጎበኙበት ወቅት እንደ ገለጹት የመቁጠሪያዋ ማሪያም በግልጸቱ ወቅት ለ3 እረኞች ያስተላፈችው መልእክት  የወቅቱን አስቸጋሪ ሁኔታ ከመገንዘቧ የተነሳ ፍቅር እንዲኖር፣ ይቅርታ መደራረግ እንዲለመድ፣ ራስን ለሌሎች መስዋዕት ማድረግ እና ራሳችንን ለሌሎች ስጦታ አድርገን ማቅረብ እንደ ሚገባ ለሦስቱ እረኛ ለነበሩ ሕጻናት አሳስባ እንደ ነበረ መግለጻቸውን ይታወሳል።

እመቤታችን ይህንን የፍቅር፣ የሰላም፣ እና የመስዋዕትነት መልእክት ያስተላለፈችው ታላላቅ ለሚባሉ የማሕበረሰብ ክፍል አባላት ሳይሆን በጊዜው በማሕበረሰቡ በጣም መጨረሻ የተባለ ስፍራ ተሰጥቶዋቸው ለነበረው እረኞች እንደ ነበረም ይታወቃል። እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም እራሱዋ ከመልአኩ ገርኤል ብስራት ቡኃላ እግዚኣብሔር በእርሷ ባከናወነው ታላቅ ነገር ስለተደነቀች “እኔን ዝቅተኛይቱን አገልጋዩን ተመልክቱዋል እና ስሙ ለዘልዓለም ቅዱስ ነው” ብላ የምስጋና መዝሙር ለእግዚኣብሔር አቅርባ እንደ ነበር ሁሉ ይህም እግዚኣብሔር በዘመናት ሁሉ ውስጥ ዝቅተኛ የተባሉ ሰዎችን ከፍ እንደሚያደርጋቸው፣ የተናቁትን እንደ ሚጎበኛቸው ለዓለም መልእክት የሚያስተላለፊያ መንግድ ነው።።

ሁላችንም እንደ ምናውቀው ሁሉም መንፈሳዊ ጉዞ የሚደረግባቸው ቤተ መቅደሶች መንፈሳዊ ህክምና የመስጫ ስፍራዎች ናቸው። በተለይም ደግም በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም ስም የተሰየሙ መንፈሳዊ ጉዞ የሚደረግባቸው ስፍራዎች ለዚህ አባባል በማሳያነት መጠቀስ የሚችሉ መንፈሳዊ ህክምና መስጫ ተቋማት ናቸው፣ ምክንያቱ በእነዚህ ቤተ መቅደሶች ውስጥ አሁንም ቢሆን መልአኩ ገብርኤል ማሪያምን ባበሰራት ወቅት ለእግዚኣብሔር የሚሳነው ነገር የለም በማለት  የተናገረው ድምጽ አሁንም በማሪያም ቤተ መቅደሶች ውስጥ በድጋሚ ስለምያስተጋባ ነው።

የማሪያም ቤተ መቅደስ የሰው ልጆች ሁሉ በመንፈስዊ ሕይወታቸው የሚያድጉበት ስፍራ ነው፣ ምክንያቱ ምዕመናንም እንደ ማሪያም እንዳልከኝ ይሁንልኝ ብለው እንዲመልሱ ስለሚረዳቸው ነው። በዚህም ስፍራ ለእግዚኣብሔር የሚሳነው ምንም ነገር የለም የሰው ልጆች ሁሉ በእግዚኣብሔር በሚተማመኑበት ወቅቶች ሁሉ ምንም የማይሳነው እግዚኣብሔር ያቀዱትን ነገሮች ሁሉ ያጎጽፋቸዋል። በእግዚኣብሔር የተማመነ ሰው በመከራዎች ውስጥ ቢገባም እንኳን ምንም የማይሳነው እግዚኣብሔር በፍቅሩ ይጎበኘዋል ለእግዚኣብሔር ርኅራኄ፣ ምሕረት፣ ፍቅር ምስጋና ይግባውና እግዚኣብሔር ከማንኛውም ዓይነት መከራ ነጻ የማውጣት ብቃት እንዳለው የምንማርበት ስፍራ ነው የማሪያም ቤተመቅደስ። እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም እግዚኣብሔር ላቀረበላት ጥሪ እንዳልከኝ ይሁንልኝ በማለት መልስ ስጥታ እንደ ነበረ ሁሉ የመቁጠሪያዋ የቅድስት ማሪያም ቤተ መቅደስ ይህንን የእግዚኣብሔር እቅድ እንድንረዳ ያግዘናል፣ ለእግዚኣብሔር የሚሳነው ነገር የለም የሚለው ሀረግ ምላሽ በምንሰጥበት ወቅቶች ሁሉ በሕይወታችን ውስጥ ታላላቅ ነገሮች ሊከሰቱ ይችላሉ።

ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮ በፖርቹጋል ሀገር በሚገኘው ፋጢማ በሚባል ስፍራ የዛሬ አንድ መቶ አመት ገደማ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም ለሦስት እረኛ ለነበሩ ሕጻናት በተገለጸችበት የመቁጠሪያዋ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም ቤተ መቅደስ ለሁለት ቀን የምቆይ መንፈሳዊ ጉዞ ለማድረግ በግንቦት 5/2009 ዓ.ም. ላይ ወደ እዚያው አቅንተው እንደ ነበረ ይታወሳል። በወቅቱ በዚሁ የመቁጠሪያዋ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም ቤተ መቅደስ ውስጥ መስዋዕተ ቅዳሴ ባሳረጉበት ወቅት ያሰሙትን ስብከት ሙሉ ይዘት እንደ ሚከተለው አስናድተነዋል፣ ተከታተሉን።  

ከዚህ ቡኃላ ታላቅ አስደናቂ ምልክት በሰማይ ታየ፣ ፀሐይን የለበሰች አንዲት ሴት ታየች፣ እርሱዋም ነብሰጡር ነበረች” (ራእይ 121) ከዚያም ኢየሱስ በወንጌል ለደቀ መዝሙሩይችውልህ እናትህ!” (ዩሐንስ 1927) አለው። እናት አለን። እውነት ነው የምላችሁ እናት አለን! የዛሬ መቶ አመት ማሪያምን ያዩዋት እረኞች እንደ ገለጹትበጣም የምታምርእናት አለን። በዛን ምሽት ዣሽንታ (.. በግንቦት 13/1917 .. ማሪያም ከተገለጸችላቸው ሕጻናት አንዱዋ ናት) ያየችውን ምስጢር ደብቃ መያዝ ስላልቻለች ለእናቷዛሬ እመቤታችንን አየዋትበማለት ነገረቻት። ሰማያዊቷን እናት አይተዋት ነበር። ብዙ ሰዎች ይህንን ግልጸት ለመጋራት ፈልገው ነበር፣ ነገር ግን ማሪያምን አላዩዋትም ነበር። ቅድስት ድንግል ማሪያም እዚህ የመጣችው ለመታየት ፈልጋ አይደለም። ወደ መንግሥተ ሰማይ በምንሄድበት ወቅት ለዘለዓለም እናያታለን።

የእምቤታችን ትንቢት የምያስጠነቅቀን እግዚኣብሔር የለሽ ሕይወት እንዳንኖር እና ፍጡራን እግዚኣብሔርን እናዳያረክሱት ማስጠንቀቅ ነው። ብዙን ጊዜ የዚህ ዓይነት ሕይወት ወደ ገሀነም እሳት የመምራት አደጋ አለው። ማሪያም የተገለጸችው የእግዚኣብሔር ብርሃን በውስጣችን እንዳለ ልትገልጽ እና ልትጠብቀን ልክ የመጀመሪያው ምንባብ ስነበብ እንደ ሰማነውልጇ ግን ወደ እግዚኣብሔር እና ወደ ዙፋኑ ተወሰደ” (ራእይ 125) የሚለውን ለማስረዳት ነው። ከሉቺያ (.. በግንቦት 13/1917 .. ማሪያም ከተገለጸችላቸው ሕጻናት አንዱዋ ናት) ታሪክ መረዳት እንደተቻለው እነዚህ ሦስቱ ሕጻናት ከእመቤታችን ቅድስት ድንግላ ማሪያም በመነጨው የእግዚኣብሔር ብርሃን ተከበው እንደ ነበረ ያትታል። እግዚኣብሔር በሰጣት ብርሃን ጋርዳቸው ነበር። ሁሉም ባይሆኑም እንደ ብዙኅኑ መንፈሳዊ ተጓዥ ምዕመናን ተመኩሮ እና ልምድ የፋጢማዋ ማሪያም ከዚህም በበለጠ ሁኔታ በልብሶቹዋ እንደምትጋርደን ያስተምሩናል። በማሪያም ጥበቃ ሥር ራሳችንን በማድረግ ቅድስት ድንግል ማሪያም ሆይ ኢየሱስን መመልከት እንድንችል አስተምሪን ብለን ልንጠይቃት ይገባል።

ውድ መንፈሳዊ ተጓዥ ምዕመናን እናት አለን። እንደ ሕጻን ልጅ በእርሷ ላይ ዘንበል በምንልባቸው ወቅቶች ሁሉ በኢየሱስ ላይ መሰረቱን ባደረገ ተስፋ እንሞላለን። በሁለተኛነት ሲነበብ የሰማነው ምንባብበአንዱ በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት የእግዚኣብሔርን ብዙ ፀጋ ተቀብለው የጸደቁ ሁሉ በድል አድራጊነት ሕይወት ይኖራሉ” (ሮም 517) ይለናል። ኢየሱስ ወደ ሰማይ ባረገበት ወቅት ከቅድስት ድንግል ማሪያም የነሳውን ሰባዊነታችንን ወደ ሰማያዊው እግዚኣብሔር ወሰደ። እስቲ እንደ አንድ ተዋኒያን ራሳችንን በመቁጠር በእግዚኣብሔር አብ ቀኝ እንደ ተቀመጥን አድርገን ተስፋ እናድርግ። ይህ ተስፋችን ሕይወታችንን ይምራው! ይህም ተስፋ ነው ሁልጊዜም እየማራን የሚገኘው።

እዚህ የተሰበሰብነው በዚህ ተስፋ በመሞላት በባለፉት መቶ አመታት ውስጥ ልዩ ልዩ ጸጋዎችን የሰጠንን እግዚኣብሔ ለማመስገን ነው። ሁሉም ሰዎች ከማሪያም መጎናጸፊያ በሚመነጨው ብርሃን ሥር በማለፍ ወደ አራቱም የዓለም መዕዘናት አስረጭተዋል። እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም ተገልጻላቸው የእግዚኣብሔርን ጥልቅ የሆነ ብርሃን እና እርሱን እንድያመልኩ በልግጸቱ ወቅት ያስተማረቻቸውን የቅዱስ ፍራንቸስኮን እና የቅድስት ዣሽንታን አብነት በመከተል ይኖርብናል። ዘወትር ለኃጢያተኞች በሚያደርጉት ጸሎት እና በመንበረ ታቦት ውስጥ በስውር የሚገኘውን ኢየሱስን ለመቀበል በሚያሳዩት ፍላጎት ምክንያት እግዚኣብሔር በቋሚነት በሕይወታቸው ውስጥ ነበረ።

በእርግጥ እግዚኣብሔር የፈጠረን ለሌሎች የተስፋ ምንጭ እንድንሆን ነው። ሁላችንም የተሰጡንን ኃላፊነቶች ትክክለኛ በሆነ መንገድ እንድንወጣ ይጠይቀናል ያሳስበናልም። በማሪያም ጠባቂነት ትክክለኛው የሆነውንና በፋሲካ የበራውን የአዳኛችን የኢየሱስን የፊት ገጽታ በማሰላሰል ለዓለማችን ዘብ መቆም ይኖርብናል። በዚህም መልኩ ሚስዮናዊ በምትሆንበት ጊዜያት ሁሉ የሚበራውን፣ እንግዳ ተቀባይ፣ ነጻ፣ ድኽ ነገር ግን በፍቅር የበለጸገች ወጣት እና ውብ የሆነውን የቤተ ክርስቲያን ፊትን በድጋሚ እንድንመለከት ትርዳን

በወቅቱ እረኞች ለነበሩ ሦስት ሕፃናት እንደ ጎርጎሮሳዊያኑ የቀን አቆጣጠር የዛሬ 100 ዓመት ገደማ በግንቦት 13/1917 ዓ.ም. በፖርቱጋል በሚገኘው ፋጢማ በሚባለው አከባቢ ልዩ ስሙ ኮቫ ዳ ኢራ በተባለው ሥፍራ ለሶስት ታዳጊ የከብት ጠባቂ እረኞች ለነበሩ ሕፃናት ፍራሲሽኮ፣ ዣሺንታ ማርቶ እና ሉሲያ ለተባሉ ሦስት ታዳጊ ለነበሩ ልጆች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያ የተገለጸችላቸው መሆኑ የሚታወቅ ሲሆን በወቅቱ የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት የነበሩት ፒዮስ ሰባተኛ እንደ የአውሮፓዊያን የቀን አቆጣጠር በግንቦት 13/1946 ዓ.ም. የእዚህን ግልጸት ትክክለኛነት ከመረመሩ ቡኃላ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም ሥም የንግደት ሥፍራ ይሆን ዘንድ ቤተ መቅደስ እንዲሠራ ፈቃድ መስጠታቸውና እስከ ዛሬም ድረስ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ምዕመናን በሥፍራው ንግደት በማድረግ እንደ ሚገኙም ይታወቃል።

ይህንን ግልጸት ከተቀበሉት ሦስቱ እረኛ ሕጻናት ውስጥ ሁለቱ ፍራንቸስኮ እና ዣሽንታ ማርቶ የተባሉት ሁለት ታዳጊ እረኞች ለነበሩ ሕፃናት  በግንቦት 5/2009 ዓ.ም. እንደ በርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮ የቅድስና ማዕረግ የተሰጣቸው መሆኑ የሚታወቅ ሲሆን ሦስተኛው እና በገዳም ሕይወት የኖሩ እና እንደ ጎርጎሮሳዊያኑ የቀን አቆጣጠር 2005 ከእዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ሲስተር ሉሲያ የሕይወት ታሪካቸው በመጠናት ላይ እንደ ሆነ ለመረዳት ተችሉዋል።

በወቅቱ ፖርቹጋል እና የተቀረው ዓለም በጦርነት ውስጥ በነበሩበት ወቅት የመቁጠሪያዋ እናታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም ለእነዚህ ሦስት እረኛ ሕጻናት በመገለጸ ሁሉም የዓለም ሕዝቦች ንስሐን በመግባት እና የመቁጠርያን ጸሎት አዘውትረው በመጸለይ ለዓለም ሰላም እንዲመጣ መጣር እንዳለባቸው ቅድስት ድንግል ማሪያም ባሳሰበችሁ መሰረት ዛሬም ቢሆን በሚልዮን የሚቆጠሩ ነጋዲያን በፖርቹጋል ሀገር ፋጢማ በሚባለው ስፍራ በመገኘት ሰላም በግለሰብ ደረጃ እና ብሎም በመላው ዓለም ሰላም ይወርድ  ዘንድ በእናታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም አማላጅነት ጸሎታቸውን ወደ እግዚኣብሔር እያሳረጉ ይገኛሉ።

ከእነዚህም ነጋዲያን መካከል በግናባር ቀደምትነት የሚጠቀሱት እና ብዙን ጊዜ ወደ ፋጢማ ንግደት በማድረግ የሚታወቁት ቅዱስ ዩሐንስ ጳውሎስ ሁለተኛ ይገኙበታል። ቅዱስ የሐንስ ጳውሎስ ሁለተኛ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት በነበሩበት ወቅት ለሳምንታዊው የጠቅላላ አስተምህሮ ምዕመናን እና የሀገር ጎብኚዎች በተገኙበት በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ በሚዘዋወሩበት ወቅት መሐመድ አሊ በተባለ ቱርካዊ እንደ አውሮፓዊያን የቀን አቆጣጠር በግንቦት 13/1981 ዓ.ም. አራት ጊዜ በጥይት ተመተው የወደቁበት ቀነ፣ የመቁጠሪያዋ ማሪያም ለእነዚህ ሦስት ሕጻናት እረኞች ከተገለጠችበት ቀን ጋር በመገጣጠሙ ከእዚህ ክፉ አደጋ ከሞት የተረፍኩት በፋጢማዋ ቅድስት ድንግል ማሪያም አማላጅነት ነው ብለው አምነው እስከ ሕይወታቸው ፍጻሜ ድረስ ከፍተኛ የሆነ አክብሮት እና ፍቅር ለቅድስት ድንግላ ማሪያም በማሳየት ይህንንም እምነታቸውን የመቁጠሪያን ጸሎት አዘውትረው በመጸልይ ተግብረውታል።

እንደ አውሮፓዊያን የቀን አቆጣጠር በግንቦት 13/2000 ዓ.ም ቅዱስ ዩሐንስ ጳውሎስ ሁለተኛ ለመጨረሻ ጊዜ ቅድስት እናታችን ማሪያም የተገለጠችበትን የፋጢማን ቅዱስ የንግደት ስፍራ መጎብኘታቸው እና እናታችን ቅድስት ድንግል ማሪያም በሕይወታቸው ላደረገችላቸው ጥበቃ እና አማላጅነት ምስጋናን አቅርበው እንደ ነበር ይታወቃል። በእዚህ የመጨርሻ ጉብኚታቸው ወቅት እንደ አውሮፓዊያን የቀን አቆጣጠር በግንቦት 13/1917 ዓ.ም ቅድስት ድንግል ማሪያም ከተገለጸችላቸው ሦስት ሕጻናት እረኞች መካከል ብቸኛዋ በሕይወት የነበረችሁ ሉቺያ በእለቱ እንደ ነበርች እና ከእዚያም ከጥቂት ዓመታት በኋላ እንደ ጎርጎሮሳዊያኑ የቀን አቆጣጠር በ2005 ዓ.ም ከእዚህ ዓለም በሞት መለየታቸው የሚታወቅ ሲሆን ሕይወታቸው ታላቅ ምስክርነትን ጥሎ ያለፈ ወቅት እንደነበር ይታወሳል።

 

 

 








All the contents on this site are copyrighted ©.