2018-01-31 14:04:00

የእግዚኣብሔር ቃል ከጆሮዋችን ወደ ልባችን ከልባችን ወደ እጃችን በመጓዝ መልካም ተግባራትን እንድናከናውን ይረዳናል


ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮ ዘወትር ረዕቡ እለት በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለሚሰበሰቡ ምዕመናን እና የሀገር ጎብኝዎች  በተለያዩ አርእስቶች ላይ ተመርኩዘው የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ እንደ ሚያደርጉ ይታወቃል። የዚሁ መርሃ ግብር አንዱ አካል በሆነው በዛሬው እለት ማለትም በጥር 23/2010 ዓ.ም. ከእዚህ በፊት በመስዋዕተ ቅዳሴ ዙሪያ በተከታታይ አድርገው የነበረ አስተምህሮ ቀጣይ ክፍል እንደ ነበረ የተገለጸ ሲሆን ከእዚህ ቀደም በመስዋዕተ ቅዳሴ ስነ-ስረዓት ዙሪያ ላይ ትኩረታቸውን በማድረግ በእዚሁ የመስዋዕተ ቅዳሴ ስነ-ስረዓት ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ ከፍተኛ መንፈሳዊ ትርጉም ያቸውን ክፍሎች በማንሳት አስተምህሮ ማድረጋቸውን ከቅድም ሲል መዘገባችን ይታወሳል። በእዚህም መሰረት ቀደም ባሉት ጊዜያት በመስዋዕተ ቅዳሴ የመግቢያ ስነ-ስረዓት ላይ ስላለው የኑዛዜ ጸሎት፣ በመቀጠልም አሁንም በመስዋዕተ ቅዳሴ የመግቢያ ስነ-ስረዓት ላይ ስላለው የመግቢያ ጸሎት አንስተው ሰፊ የሆነ ትንታኔ መስጠታቸው የሚታወቅ ሲሆን በዛሬው ቀን ደግሞ ከእዚሁ የመግቢያ ጸሎት በመቀጠል የሚገኘውን የመጽሐፍ ቅዱስ ንባባትን በተመለከተ ሰፊ አስተምህሮ አድርገዋል። የእግዚኣብሔር ቃል በሕይወታችን የሚያደርገው ጉዞ በተመለከተ የትናገሩት ቅዱስነታቸው የእግዚኣብሔር ቃል ከጆሮዋችን ወደ ልባችን ከልባችን ወደ እጃችን በመጓዝ መልካም ተግባራትን እንድናከናውን ይረዳናል ማለታቸውም ተገልጹዋል።

ክቡራን እና ክቡራት የዝግጅቶቻችን ታዳሚዎች ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮ በዛሬው እለት በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰቡ ምዕመናን እና የሀገር ጎብኝዎች ያደርጉትን የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ሙሉ ይዘቱን እንደ ሚከተለው ተርጉመነዋል አብራችሁን በመሆን እንድትከታተሉን ከወዲሁ እንጋብዛለን።

የተከበረቻሁ ወንድሞቼ እና እህቶቼ እንደምን አረፈዳችሁ!

በስርዓተ ቅዳሴ ዙሪያ ማድርግ የጀመርነውን የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ዛሬ እንቀጥላለን። ከእዚህ በፊት ያደርግነውን አስተምህሮ ያቆምነው በመስዋዕተ ቅዳሴ መግቢያ ስነ-ስረዓት ላይ ነበር። ዛሬ ደግሞ የእዚሁ የመስዋዕተ ቅዳሴ ስነ-ስረዓት አንዱ ክፍል የሆነውን የእግዚኣብሔር ቃል የሚነበብበትን ክፍል እንመለከታለን። ይህም በጣም ገንቢ የሆነ ክፍል ሲሆን፣ እግዚኣብሔር ያደረገውን እና እያደርገ የሚገኘውን ነገሮች የምናዳምጥበት ክፍል ነው። ይህም ከእግዚኣብሔር በቀጥታ የሚመጣ ቃል ነው እንጂሲባል ሰምቻለሁ ተብሎ የሚነገር ቃል አይደለም፣በቤተ ክርስትያን ውስጥ ቅዱሳን መጽሐፍት ሲነበቡ እግዚኣብሔር ራሱ በቀጥታ ለሕዝቡ ይናገራል፣ ክርስቶስም ቅዱስ ወንጌል በሚነበብበት ወቅት  በእነዚህ ቃላት ውስጥ ሕያው ይሆናል።

ብዙን ጊዜ የእግዚኣብሔር ቃል በሚነበብበት ወቅት የተለያዩ ያለተገቡ አስተያየቶችን እንሰጣል፣ ተመልከት ይህንን ተመለከት ያንን፣ ተመለከት ያንን የመነበረ ታቦት አገልጋይ . . .ይህን እና ይህንን የመሳሰሉ አስተያየቶችን እነሰጣል አይደል? እውነት አይደለም እንዴ ? እውነት ነው። የእግዚኣብሔር ቃል በቤተክርስቲያን ውስጥ በሚነበብት ወቅት ብዙን ጊዜ ወሬ እናወራለን። ነገር ግን የእግዚኣብሔር ቃል በሚነበብበት ወቅት አስተያየት መስጠት ካለብን በተነበበው የእግዚኣብሔር ቃል ላይ ተመስረቶ ብቻ መሆን ይገባዋል። የእግዚኣብሔር ቃል በሚነበብበት ወቅት አንደኛው ምንባብ፣ ሁለተኛው ምንባብ፣ መዝሙረ ዳዊት ከእዚያም ቅዱስ ወንጌል ይነበባል። ይህ በሚሆነበት ወቅት ታዲያ የሚናገረን እግዚኣብሔር በመሆኑ የተነሳ፣ ልባችንን ከፍተን ማዳመጥ እንጂ ሌላ ነገር መናገር አይደግባንም።

ይህንን ሐሳብ በተሻለ መልኩ እንድትረዱ እስቲ በደንብ ላብራራው። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙ የመጽሐፍ ቅዱስ ገጾች የእግዚአብሔር ቃል በመሆናቸው የተነሳ  ሕያው የሆኑ መልእክቶችን ያስተላልፋሉ። እግዚኣብሔር ራሱ ነው በእነዚህ ቅዱስ በሆኑ ቃላት አማካይነት በእመነት በምንሰማበት ወቅት ቃሉ በሕይወታችን ህያው እንዲሆን የሚያደርገውም እርሱ ነው። መንፈስ ቅዱስበነቢያት አማካይነት ተናግሮ ነበር፣ መነፍስ ቅዱስ የመጽሐፍ ቅዱስ ጸሐፊዎች ላይ እስትፋሱን አሳድሮባቸው ነበር፣ ይህ "የእግዚአብሔር ቃል በጆሮው ውስጥ እና በልባችንም ውስጥ ሳይቀር የሚሠራ መሆኑን" ያረጋግጥልናል። ነገር ግን የእግዚአብሔርን ቃል ለመስማት የተከፈተ ልብ ያስፈልጋል። እግዚኣብሔር ይናገራል እኛም ማዳመጥ ይገባናል፣ ይህንን ያዳመጥነውን ቃል ደግሞ በሰማነው መጠን በተግባር ላይ ማዋል ይገባናል። ማዳመጥ በጣም አስፈላጊ የሆነ ነገር ነው። አንድ አንድ ጊዜ የሚነበቡልን የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባባት ጠንከር ያሉ በመሆናቸው የተነሳ፣ ለመረዳት ያስችግረን ይሆናል፣ በዝምታ እና በስሜት ለማዳመጥ በምንሞክረበት ግዜ ሁሉ  እግዚኣብሔር ለየት ባለ ሁኔታ ለእኛ ልያስረዳን ይችላል። በመስዋዕተ ቅዳሴ ወቅት የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባባት በሚነበቡበት ወቅት የሚናገረን እግዚኣብሔር ራሱ መሆኑን በፍጹም መርሳት የለባችሁም።

መስማት በጣም አስፈላጊ ነገር ነው። በእርግጥ ኢየሱስም፣ “ ‘ሰው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣው ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርምተብሎ ተጽፎአል” እናዳለው ሁሉ ይህ የሕልውና ጥያቄ ጭምር ነው። ሕይወት የሚሰጠን የእግዚኣብሔር ቃል ነው። በዚህ መልኩ በመስዋዕተ ቅዳሴ ወቅት ስለ ሚነበበው የእግዚኣብሔር ቃል ስናወራ መነፈሳዊ ሕይወታችንን እና ሕይወታችንንም ሳይቀር የሚመግብ ቃል ነው። በእርግጥ ከብልይ ኪዳን እንዲሁም ከአዲስ ኪዳንም ሳይቀር በመነበብ ሕይወታችንን በሚገባ ይመግባታል። እስቲ እነዚህ በስርዓት ቅዳሴ ወቅት የሚነበቡልን የእግዚኣብሔር ቃላት ያላቸውን ክብደት እናስብ፣ በወቅቱ የሚነበቡት ምንባባት ከቅዱስ ወንጌል ጋር በመጣመር ስርዓተ አምልኮዋችንን የተሟላ ያደርጉታል። በመስዋዕተ ቅዳሴ ወቅት የሚነበቡልን የእግዚኣብሔር ቃላት በእለቱ ከሚዘመሩት መዝሙሮች ጋር በመጣመር በቤተ ክርስትያን ውስጥ ሕብረትን በመፍጠር ሁላችንንም በጉዞዋችን ያጅቡናል።

አንድ አንድ ጊዜ ከእግዚኣብሔር ቃል አስቀድመን የእለቱን ጋዜጣ ለማንበብ እንሽቀዳደማለን። እንዲህ ማድረግ ግን በፍጹም አይገባም። ጋዜጣ የእለቱ ዜና ነው፣ በመስዋዕተ ቅዳሴ ወቅት የምንሰማው ደግሞ የእግዚኣብሔር ቃል ነው። ሰለእዚህ ለእግዚኣብሔር ቃል ቅድሚያ በመስጠት ይኖርብናል ከእዚያ የእለቱን ጋዜጣ ማንበብ እንችላለን። ነገር ግን ይህንን የእግዚኣብሔር ቃል በሌላ ነገር መተካት ግን በሰዎች እና በእግዚኣብሔር መካከል ያለው ውይይት ላይ ጥላ ያጠላል። በተመሳሳይ መልኩም የእግዚኣብሔር ቃል የሚነበብበት ቦታ ከፍተኛ ክብር ሊሰጠው ይገባል፣ የእግዚኣብሔርን ቃል የሚያነቡ ሰዎች ደግሞ ተዘጋጅተው በደንብ ማንበብ ይኖርባቸዋል። በእዚህም አግባብ የእግዚኣብሔርን ቃል በመስዋዕተ ቅዳሴ አወቅት የሚያነቡ ሰዎች በቅድሚያ ዝግጅት ማድረግ ይኖርባቸዋል።

የእግዚኣብሔር ቃል እንዳንጠፋ የሚረዳን በጣም አሰፈላጊ መሆኑን የምናውቅ ይመስለኛል። “ሕግህ ለእግሬ መብራት፣ ለመንገዴም ብርሃን ነው ይለናል (መዝ.119፡105) ይላል። በስርዓተ አምልኮ ውስጥ የቀረቡትን  የእግዚአብሔር ቃሎች መደበኛ በሆነ መልኩ ካልተመገብን በስተቀር  በምድራዊ ጉዞዎቻችን የሚገጥሙንን አስቸጋሪ ነገሮችን እና  ፈተናዎች ልንጋፈጥ የምንችለው እንዴት ነው?

በእርግጥ ይህንን የእግዚኣብሔርን ቃል በጆሮ ብቻ መስማት በቂ አይደለም፣ ይህ መለኮታዊ የሆነ ዘር በልባችን ውስጥ በማስገባት መልኮታዊ የሆነ ፍሬ እንዲያፈራ ማድረግ ይገባል። በማርቆስ ወንጌል 4፡14-20 ላይ የተጠቀሰውን የዘርውን ምሳሌ በማስታወስ የተዘራው ዘር ያረፈበትን የተለያየ ስፍራ ማስታወስም ይገባል።

መንፈስ ቅዱስ ነው በቅድምያ በሕይወታችን ውስጥ ያለውን ዘር ፍሬ እንዲያፈራ የሚያደርገው እርሱ ነው፣ ነገር ግን መነስ ቅዱስ ገብቶ የሚሰራበት ልብ ያስፈልገዋል፣ በእዚህም ረገድ ቅዱስ ሐዋሪያው ያዕቆብ እንዲህ ይለናል “ቃሉ የሚናገረውን አድርጉ እንጂ ሰሚዎች ብቻ ሆናችሁ ራሳችሁን አታታልሉ” (የያዕቆብ መልእክት 1፡22)። የእግዚአብሔር ቃል በውስጣችን ጉዞ ይጀምራል። በጆሮዋችን እናዳምጥ፣ በጆሮዋችን ውስጥ ብቻ እንዳይቀር ወደ ልባችን እናስገባው፣ አሁንም በልባችን ውስጥ ብቻ እንዳይቀር ወደ እጃችን እናውረደው ከእዚያም ወደ መልካም ሥራ እንለውጠው። የእግዚኣብሔር ቃል በሕይወታችን የሚያደርገው ጉዞ ይህ ነው ከጆሮዋችን ወደ ልባችን ከልባችን ወደ እጃችን። እነዚህን ነገሮች ለመማር እንሞክር። አመሰግናለሁ።

ክቡራን እና ኩብራት አንባቢዎቻችን  ይህ ቀደም ሲል የታደማችሁት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮ በዛሬው እለት በቫቲካን በሚገኘው በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ ለተሰበሰቡ ምዕመናን ያደርጉትን የትምህርተ ክርስቶስ አስተምህሮ ሙሉ ይዘት ነበር።

 

 

 

 








All the contents on this site are copyrighted ©.