2018-01-09 09:43:00

በቅድስት መንበር፣ የሕዝቦች ሁለ ገብ ማሕበራዊ እድገት መምሪያ፣ የአንድ ዓመት የሥራ ሂደቱን ገመገመ።


በቅድስት መንበር፣ የሕዝቦች ሁለ ገብ ማሕበራዊ እድገት መምሪያ፣ የአንድ ዓመት የሥራ ሂደቱን ገመገመ   

በቅድስት መንበር ባዲስ መልክ ከተቋቋሙ ሐዋርያዊ ጽሕፈት ቤቶች መካከል አንዱ የሆነው የሕዝቦች ሁለ ገብ ማሕበራዊ እድገት ሐዋርያዊ ጽሕፈት ቤት፣ ከተቋቋመበት ከአንድ ዓመት የሥራ ሂደት በኋላ ያከናወናቸውን አገልግሎቶቹን በዝርዝር ተመለከተ። ጽሕፈት ቤቱ  ቅድስት መንበር በመላዋ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ውስጥ በምታካሂደው የተሃድሶ እቅዶቿ መሠረት ከተቋቋሙት ማዕከላዊ ጽሕፈት ቤቶች መካከል አንዱና ዋናውን ቦታ የያዘ እንደሆነ ይታወቃል። ሐዋርያዊ ጽሕፈት ቤቱ በታህሳስ ወር 2010 ዓ. ም. ሥራውን ሲጀምር፣ የፍትህና ሰላም፣ የሕዝቦች ሁለ ገብ ማሕበራዊ እድገት፣ የስደተኞችና ጥገኝነት ጠያቂዎች ሐዋርያዊ አገልግሎት፣ የመንገደኞች አገልግሎትና የጤና አገልግሎት ሐዋርያዊ ምክር ቤቶችን ያጠቃልላል። ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ይህን ሐዋርያዊ ጽሕፈት ቤት በበላይነት እንዲመሩ ብጹዕ ካርዲናል ፒተር ታርክሰንን መሰየማቸው ይታወቃል።

ብጹዕ ካርዲናል ፒተር ታርክሰን፣ ከአንድ ዓመት የሥራ ጊዜ በኋላ ባቀረቡት ሪፖርታቸው፣ ቀዳሚው ተግባር የነበረው በመጀመሪያ ለማሕበራዊ እድገት ስኬታማነት አገልግሎት የሚሰጡ መምሪያዎችን ማሰባሰብ፣ በሁለተኛ ደረጃ በውስጡ የሚሠሩ ሰራተኞችን ማደራጀት፣ በሦስተኛ ደረጃ በመገልገያ መሳሪያዎች የተሟሉ ቢሮዎችን መክፈትና መደበኛ ሥራን ማስጀመር ነው ብለዋል።

ካርዲናል ፒተር በሪፖርታቸው፣ እስካሁን በመላው ዓለም ከሚገኙ ጳጳሳዊ ምክር ቤቶችና ቤተክርስቲያን ጋር በርካታ ስብሰባዎችን እንዳደረጉና በማድረግም ላይ እንዳሉ ተናግረው ይህም ሐሳቦቻቸውን ለመጋራት እንደጠቀማቸው አስረድተዋል። ካርዲናል ፒተር በማከልም ከጳጳሳት ምክር ቤቶች ጋር ስንገናኝ በቀዳሚነት የሚደረገው ውይይትም፣ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በ2007 ዓ. ም. አካባቢያዊ ጉዳዮችን አስመልክተው ባስተላለፉት  መልዕክት ላይ ሲሆን ካርዲናሉ እንደገለጹት አሁንም ከተቀሩት በርካታ ጳጳሳዊ ምክር ቤቶች ጋር ስብሰባ ማድረግ እንደሚገባ ገልጸዋል። በዚህ ርዕስ ላይ ሰፋ ያለ ጊዜ ወስደን እንድንወያይበት ከሚያስገድዱን ምክንያቶች አንዱ በርዕሡ ዙሪያ የተሰበሰቡት ሃሳቦች በዓለም ዙሪያ ከሚገኙ ሀገረ ስብከቶችና ቁምስናዎች የተሰበሰቡ እንደመሆናቸው፣ ተመልሶም የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ መልዕክት በጳጳሳት ምክር ቤቶች በኩል ወደ ቁምስናዎች እንዲደርስ መልካም መንገድ ስለሚፈጥር ነው ብለዋል። በጉዳዩ ላይ የአንድ ወገን የበላይነት እንዲታይ ሳይሆን ከሁለቱም ወገን የሚፈልቁ የጋራ ሃሳቦችንና አስተያየቶችን በመመልከት ስምምነት ላይ ለመድረስ ስለሚያስችል ነው ብለዋል።

በተጨማሪም ካርዲናል ፒተር፣ በጽሕፈት ቤታችው ውስጥ ያሉት ሰራተኞች ሥራቸውን በስኬታማነት ለማከናወን ያስችላቸው ዘንድ ለቢሮ ሃላፊዎች በሙሉ፣ ባለሞያዎች የታገዘ ግንዛቤን ማስጨበጥ ሥራ እንድሚያስፈልግ ገልጸው ቀጥሎም በቢሮ መሪዎች በኩልም በውስጡ ለተካተቱ ሰራተኞች መልዕክት ለማስተላለፍ ያግዛል ብለዋል።

ይህን ሐዋርያዊ አገልግሎት ፍሬያማ ለማድረግ የገንዘብ ድጋፍ እንደሚያስፈልግ ተናግረው ጽሕፈት ቤታቸው የገንዘብ አቅማቸውን ማሳደግ የሚችሉበትን መንገድ እያመቻቸ እንደሆነ ገልጸው፣ በደቡቡ የዓለማችን ክፍሎች የገንዘብ አቅም የተመናመነ ቢሆንም ሐዋርያዊ አገልግሎት በስፋት እንደጨመረ ገልጸው፣ ካርዲናል ፒተር፣ ጽሕፈት ቤታቸው፣ በመላው ዓለም የሚገኙ ቁምስናዎች እርዳታ ጠባቂ ሆነው እንዳቀሩ የገንዘብ አቅማቸዉን የሚያሳድጉበትን መንገዶች ለመጠቆም እቅድ እንዳለው ተናግረዋል። የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስን መልዕክት በማስታወስ፣ ገንዘብ የሰዎችን ችግር እንዲያቃልል እንጂ ሰው የገንዘብ ተገዢ መሆን የለበትም ብለዋል። በዚህም መሠረት ቁምስናዎች በገንዘብ አቅም ራሳቸውን እንዲችሉ የሚያግዙ 3 ተከታታይ ሴሚናሮችን ለመስጠት መዘጋጀታቸዉን ገልጸዋል።               

      








All the contents on this site are copyrighted ©.