2017-05-28 16:03:00

"ወደ ዓለም ሕዝብ ሁሉ ሂዱ በአብና በወልድ፣ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኃቸው የእኔ ደቀ መዛሙርት አድርጉዋቸው"።


ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንቸስኮ በግንቦት 19/2009 ዓ.ም. በሴሜን ጣሊያን በሚገኘው የሊጉሪያ ክልል ዋና ከተማ በሆነችው ጄኖቫ የአንድ ቀን ሐዋሪያው ጉብኝት ማድረጋቸው ይታወቃል። በዚህ ለአንድ ቀን በቆየው ሐዋሪያዊ ጉብኝት ለቅዱስነታቸው ከተዘጋጀው የጉዞ መርሃ ግብር መሰረት በቀዳሚነት ከጄኖቫ የሠራተኞች መሕበራት አባላት ጋር ተገናኝተው ተወያይተዋል። በመቀጠልም ከሊጉሪያ ክልል ከተወጣጡ ጳጳሳት፣ ካህናት፣ ገዳማዊያን/ዊያት፣ እንዲሁም ከዘርዐ ክህነት ተማሪዎች ጋር ተገናኝተው ተወያይተዋል።

በተጨማሪም  በጄኖቫ የሚገኘውን ጃኒና ጋዝሊን የተባለውን የሕጻናት ሆስፒታል በመጎብኘት ከሕጻናቱ እና ከወላጆቻቸው ጋር ቆይታን ማድረጋቸው የታወቀ ሲሆን በመጨረሻም እንደ አውሮፓዊያኑ የቀን አቆጣጠር 1963 ዓ.ም. በ46 አመታቸው በሰው እጅ የተገደሉት የመጀመሪያው ካቶሊክ የአሜርካን ፕሬዚዳንት በነበሩት ጆን ኤፍ ኬኔዲ ስም በተሰየው አደባብይ ላይ መስዋዕተ ቅዳሴን አሳርገዋል። ቅዱስነታቸው በዚሁ ባሳረጉት መስዋዕተ ቅዳሴ ላይ ያሰሙትን ስብከት ሙሉ ይዘቱ እንደ ሚከተለው ተርጉመነዋል።

በእለቱ የተነበቡት ምንባባት

  1. < > ሥራ 11-11 < > 117-23 < > 2816-20ዛሬ በተነበበል የወንጌል ቃል እንደ ሰማነው ኢየሱስ ወደ ሰማይ ከማረጉ በፊት ለደቀ መዛሙርቱ “ሥልጣን ሁሉ በሰማይ እና በምድር ተሰቶኛል” (ማቴ 28፡18) ብሎ ተናግሮ እንደ ነበረ ሰምተናል። የኢየሱስ ስልጣን የእግዚኣብሔር ኃይል ነው። በዛሬ ምንባባት ውስጥ በቀዳሚነት የምናገኘው ቁልፍ የሆነ ቃል ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ “አብ በገዛ ሥልጣኑ የወሰነውን ጊዜ እና ዘመን እናንተ ልታውቁ አትችሉም” ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ በእናንተ ላይ በወረደ ጊዜ ኃይልን ትቀበላላችሁ” (የሐዋሪያት ሥራ 1፡7,8) በማለት ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ የተናገረው ቃል የመጀመሪያው ቁልፍ የሆነ ቃል ሲሆን  በሁለተኛው ምንባብ ውስጥ ደግሞ ሐዋሪያው ጳውሎስ “ለእኛ ለምናምነው ያዘጋጀው ኅይል ምን ያህል ታላቅ መሆኑን” እና “ይህም በእኛ የሚሠራ ታላቅ ኅይል” (ኤፌሶን 1፡19) መሆኑን ይነግረናል። ነገር ግን ይህ የእግዚኣብሔር ኅይል እና ሥልጣን ምንድን ነው?

     

    ኢየሱስ ይህ ሥልጣን “የሰማይ እና የምድር” ሥልጣን መሆኑን ያረጋግጥልናል። ከሁሉም በላይ ደግሞ ይህ ሥልጣን ሰማይን እና ምድርን የሚያገናኝ ሥልጣን ነው። ዛሬ ይህንን ምስጢር የምናከብርበት ማንኛው ምክንያት ኢየሱስ ወደ ሰማይ በሚያርግበት ወቅት የእኛ ሥጋዊ አካላችን ከሰማይ ደፍ ተሻግሩዋል፣ ሰባዐዊነታችን በዚያ ከእግዚኣብሔር ጋር ለዘላለም ይኖራል። መተማመኛችንም እርሱ ነው፣ ምክንያቱም እግዚኣብሔር መቼም ቢሆን ከሰው ስለ ማይለይ ነው። ከእግዚኣብሔር እና ከእየሱስ ጋር የምንኖርበት ቦታ እንዳለን ማወቃችን ያጽናናል፣ “እንግዲህ ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችሁ፣ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ በተቀመጠበት ሥፍራ ያሉትን ነገሮችን እሹ፤ አሳባችሁም በላይ ባለው ላይ እንጂ በምድራዊ ነገር ላይ አይሁን!” (ቆላስይስ 3፡1,2)። ኢየሱስ በስልጣኑ ሰማይን እና ምድርን አገናኝቱዋል።

    ነገር ግን ይህ የእርሱ ሥልጣን ወደ ሰማይ በመውጣቱ የተነሳ አላበቃም፣ ዛሬም ይቀጥላል፣ ለዘልዓለም ይኖራል። በእርግጥ ኢየሱስ ወደ አባቱ ከማረጉ በፊት “እኔም እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁል ጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ” (ማቴዎስ 28፡20) ብሎ ተናግሮ ነበር። ይህም እኛ ወደ አንድ ቦታ ለመጓዝ በምንነሳበት ወቅት ሁሉ በቀላል ቋንቋ ውድ ጓደኞቼ በምሄድበት ቦታ ሁሉ አስታውሳችዋለሁ ብለን እንደ ምንናገረው ዓይነት ንግግር በፍጹም አይደለም። ኢየሱስ በእርግጥ ከእኛ ጋር እና ለእኛ ነው፣ ሁል ጊዜም ቢሆን በሰማይ ሰበብዐዊነቱ እና ሰብዐዊነታችንን ለአባቱ ያሳያል፣ ኢየሱስ ስለ እኛ ጥቅም “ሁል ጊዜ ለእኛ እየማለደ ይኖራል” (ዕብራዊያን  7፡25)። የኢየሱስ ሥልጣን ማሰሪያ ቃል የሚሆነው ማማለደ የሚለው ቃል ነው። ኢየሱስ በአባቱ ጎን በመሆን  ሁል ጊዜ በሁሉም ሁኔታ ለእኛ ያማልዳል። ማንኛውም ዓይነት ጸሎት በምናደርበት ወቅት፣ ማንኛውም ዓይነት ምሕረት በምንለምንበት ወቅት፣ በተለይም ደግሞ በስርዐተ ቅዳሴ ወቅት ኢየሱስ ጣልቃ በመግባት ለእኛ በመስዋዕትነት ያቀረበልንን ሰውነቱን እና ቁስሉን ለአባቱ በማሳየት ለእኛ ያማልድልናል። እርሱ የእኛ “ጠበቃ” ነው (1 ዩሐንስ 2፡1)፣ እኛ አንድ በጣም አስፈላጊ “ነገር” ሲገጥመን፣ እርሱን “ጌታ ኢየሱስ ሆይ ለእኔ፣ ለእኛ፣ ለእዛም ሰው፣ ለእዛ ለተከሰተው መጥፎ ሁኔታም አማልድልን” በማለት በእመነት ልናስረክበው ይገባል።

    ኢየሱስ ይህንን የማማለድ ብቃት ለእኛ እና ለቤተ ክርስትያን በመስጠት እኛም ለሌሎች እንድንጸልይ ሥልጣን እና የማማለድ ግዴታን ሰጥቶናል።  “እኛ እንደ ቤተ ክርስትያን፣ እንደ አንድ ክርስትያን አንድ ሰውን ወይም አንድ ሁኔታን ወደ እግዚኣብሔር በማቅረብ ይህንን ሥልጣን በተግባር በማዋል ጸልያለው ወይም ጸልየናል ወይ?” ብለን ራሳችንን ልንጠይቅ ይገባል። ዓለማችን ጸሎታችን ያስፈልገዋል። እኛም ራሳችን ብንሆን ጸሎት ያስፈልገናል። በእየ እለቱ እንሮጣለን፣ እንሥራለንም፣ በብዙ ነገሮችም እንጠመዳለን፣ ልክ ቁሳቁሶችን ጭኖ ረጅም እና አድካሚ ጎዞ አድርጎ ወደ ወደቡ ተመልሶ መልሕቁን ጥሎ፣ መብራቶቹን እንደ ሚያጠፋፋ አንድ መርከብ እኛም በሚመሽበት ወቅት ሰውነታችን በድካም ይዝላል፣ ነብሳችንም ይከብዳታል። በእነዚህ ሁሉ ሩጫዎች ውስጥ ሆነን፣ ምን እንደ ምንሠራ ግራ ተጋብተን፣ የት እናዳለን እንዘነጋለን፣ ራሳችንን በራሳችን ዝግ በማድረግ ወላዋይ እንሆናለን።  “የክፉ ሕይወት” ጎርፍ እንዳይወስደን በእየቀኑ “መልሕቃችንን በእግዚኣብሔር ላይ በመጣል” ሸክማችንን፣ ሰዎችንም ይሁን ሁኔታዎችን ሁሉ ወደ እርሱ በማምጣት ሁሉንም በአደራ እናስረክበው። የጸሎት ኅይል ይህ ነው፣ ሰማይንና ምድርን ማገናኘት፣ እግዚኣብሔር በእኛ ጊዜ ውስጥ እንዲገባ ማድረግ ነው። የክርስትያን ጸሎት ራሳችን በራሳችን ብቻ መልካም የሚባል ሰላም ውስጥ መኖር ማለት አይደለም ወይም የውስጥ መረጋጋት መጎናጸፍ ማለትም አይደለም፣ እኛ የምንጸልየው ሁሉንም ነገሮች ወደ እግዚኣብሔር ለማምጣት ነው፣ ዓለምን ለእርሱ አደራ ለመሰጠትም ጭምር ነው፣ ጸሎት ማለት ማማለድ ማለት ነው። መረጋጋት ሳይሆን ፍቅር ነው። ይህም መለመን፣ መፈለግ ማንኳኳትንም (ማቴ 7፡7) ያካትታል። አንዳችን ለአንዳችን በመጸለይ በአማላጅነት ተግባር ውስጥ መሳተፍ አለብን። ያለምንም ድካም ማማለድ አለብን፣ ይህም የእኛ ቀዳሚው አላፊነት ሊሆን ይገባል ምክንያቱም ዓለማችን ወደ ፊት እንዲጓዝ የሚያደርገው ጸሎት ስለሆነ ነው። ተልዕኮዋችን በጊዜው አድካሚ የሆነ ነገር ቢሆንም ቅሉ ነገር ግን ሰላም የሚሰጥ ነው። የእኛ ሥልጣን ዓለም እንደ ሚያደርገው ከሁሉም መብለጥ ወይም ከሁሉም አስበልጠን መጮኽ አይደለም፣ ነገር ግን ጦርነትን ማስቆም የሚችል እና ሰላምን የሚያጎናጽፈውን ትሁት የሆነ ጸሎት መለማመድ ነው። ኢየሱስ ከአባቱ ጎን ሆኖ ሁሌም ለእኛ እንደ ሚያማልድ ሁሉ እኛም የእርሱ ደቀ መዝሙር የሆንን ሁላችን ሰማይ እና ምድር የቀራረቡ ዘንድ ሳንታክት መጸለይ ይኖርብናል።

    በዛሬው ቅዱስ ወንጌል (ማቴ.28፡ 16-20) ውስጥ እንደ ተጠቀሰው ከመማለድ በመቀጠል የምናገኘው ቁልፍ የሆነ ቃል ማብሰር የሚለው ቃል ነው። ጌታ ደቀ መዛሙርቱን በመንፈስ ቅዱስ ኅይል ተመርተው “ስለዚህ ሂዱና ሕዝቦችን ሁሉ በአብ፣ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው” (ማቴ. 28፡19) ብሎ ይልካቸኃል። ይህም በእነርሱ ላይ ያለውን መተማመን ይገልጻል፣ ኢየሱስ እኛን ያምናል፣ እኛ ራሳችን ስለራሳችን ከምናምነው በላይ እርሱ በእኛን ያምነናል። እኛ ጉድለቶች ቢኖሩብንም እናኳን እርሱ ይልከናል፣ መቼም ቢሆን ፍጹማን እንደ ማንሆንም ያውቃል፣ ቅዱስ ወንጌልን ለማብሰር ከዚህ የተሻለ ብቃት ያስፈልገኛል ብለን ጊዜ በምንፈጅት ወቅት መቼም ቢሆን ጊዜ አናገኝም፣ አሁኑኑ መጀመር ይኖርብናል።

    ለኢየሱስ አስፈላጊ እና ዋንኛው በቅድሚያ መፈጸም የሚገባን አንድ ነገር ቢኖር ራሳችን በራሳችን ከቆለፍንበት ስፍራ መውጣ መቻል ነው። ምክንያቱም ቅዱስ ወንጌል ተቆልፎ እና ታሽጎ መቀመጥ የሚችል ጉዳይ አይደለም፣ ምክንያቱም የእግዚኣብሔር ፍቅር ተራማጅ እና ሁሉንም የሚያካትት በመሆኑ የተነሳ ነው። ስለዚህም ለማብሰር መራመድ ያስፈልጋል በተለይም ደግም ከራሳችን መውጣት ይኖርብናል። ለጌታ ተረጋግቶ መቀመጥ፣ ራሳችን  ዓለም ውስጥ በምቾት ወይም ያለፈውን ጊዜ በመናፈቅ መኖር፣ ለእርሱ በእነዚህ ስሜቶች ውስጥ መኖር እና መረጋጋት አይመቸውም። ለኢየሱስ ደኅንነት የሚገኘው በእርሱ በመተማመን በመሄድ ነው፣ የእርሱ ኅይል የሚገለጸው በዚሁ መልኩ ብቻ ነው። ኢየሱስ ሁሉም ነገር መልካም በሚሆንበት ወቅት እና ሁሉም ነገሮች በቁጥጥራችን ሥር አድርገን በምቾት እና በተድላ በመኖራችን አይደሰትም። ምክንያቱ ሁል ጊዜ እንድንወጣ እና እንድንራመድ ይፈልጋል።

    የቀድሞዎቹ ሥር መሰረታችን የነበሩ ደቀ መዛሙርት ተከታዮች እንደ መሆናችን መጠን ቅዱስ ወንጌልን የምናበስርበት የመጀመሪያው ስፍራ በዓለማችን ውስጥ በሚገኙ መንገዶች ላይ ሊሆኑ ይገባል፣ ምክንያቱም ከሁሉም ጊዜ በላይ ዛሬ ኢየሱስ  የሚታወቀው መንገዶች ላይ ስለ ሆነ ነው። ይህ የወንጌል ብስራት የሚከናወነው በዓለማችን ኅይል ሳይሆን እንደ ጥንቱ ደቀ መዛሙርት በመንፈስ ቅዱስ ኅይል በትህትናና በየዋህነት በደስታ እንዲፈጸምም ጌታ ይፈልጋል። ይህም አስቸኳይ ጉዳይ ነው። አሉባልታዎችን ሁሉ ወደ ጎን በመተው እና የማይረባ ክርክሮችን አስወግደን በአንጻሩም ለማሕበራዊ ዋስትናና ለሰላም መሥራት ይኖርብናል፣ በታላቅ ብርታት ከመቀበል ይልቅ በመስጠት ደስታ እንደ ሚገኝ ማመን ይገባናል። አማላጃችን የሆነው እና ከሙታን የተነሳው ሕያው የሆነ ጌታ፣ የጉዞዋችን ብርታት ይሁን፣ ለጉዞዋችን ጥንካሬን ይስጠን። አሜን!!








All the contents on this site are copyrighted ©.