2016-05-07 11:23:00

በአውሮፓ የሚገኙ የክርስቲያን አብያተ ክርስቲያናት ሕብረት በመጭው ግንቦት ወር ጠቅላላ ስብሰባ እንደ ሚያደርጉ ታወቀ።


በሚቀጥለው ግንቦት 1,2008 ለሚካሄደው በአውሮፓ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ጠቅላላ ስብሰባ መርህ ቃል እንዲሆን የተመረጠው “ሁላችንንም አንድ የሚያደርገን እሴቶችን እናክብር” በሚል አርዕስት ስር እንደ ሚሆን ከወዲው የተገለጸ ሲሆን በአውሮፓ ውስጥ እና ከአውሮፓ ውጭ በሚካሄዱት ግጭቶች የተነሳ እየተከሰት ባለው ያልተጠበቀ የስደተኞች ፍሰት “አውሮፓ እንደ እዚህ ቀደም ሁሉ  መለያዋ የሆነውን የሰላም፣ የዲሞክራሲ እና የሰው ልጆች መብት የማስከበር መርሀ-ግብሯን ያለማቋረጥ መቀጠል” እንደ ሚገባ ማሳሰብ በአውሮፓ የሚገኙ የክርስቲያን አብያተ ክርስቲያናት የእዚህ የያዝነው ዓመት ዋነኛው ተግባራቸው እንደ ሚሆን ከአውሮፓ አብያተ ክርስቲያናት ሕብረት የተሰጠ መግለጫ ማስታወቁ ተገለጸ።

በርካታ መሰናክሎችን፣ ፈተናዎችን  እና እንዲሁም ፈታኝ የሆነውን ዓለማቀፋዊ ግንኙነቶችን  አውሮፓ እየተጋፈጠች መሆኑ ከጽሕፈት ቤቱ የተገለጸ ሲሆን ግጭት እና ጦርነት ከአውሮፓ ወስጥ እና ከአውሮፓ ውጭ እንደ ሚመነጩ ጨምረው ገልጸዋል። ስደተኞችን የመቀበል ወይም ያለመቀበል  ውጥረት እና ቀውስ እየቀጠለ መሆኑን ያወሳው የመስሪያ ቤቱ ሪፖርት ለእነዚህ ወሳኝ ችግሮች መፍትሄ አለመገኘቱ የሚያሳየው የአውሮፓ ሀገራት በችግር ላይ የሚገኙትን ሰዎች የመርዳት ግብረ-ገባዊ እና ሕጋዊ ግዴታቸውን መወጣት አለመቻላቸውን እንደ ሚያሳይም ተወስቱዋል።

“የአውሮፓ የኢኮኖሚ እና የፖሌቲካ ሁኔታም በቀውስ ውስጥ መሆኑን” ያወሳው የመስሪያ ቤቱ ሪፖርት በዓለም ላይ የተከሰተው የኢኮኖሚ ቀውስ እና በአውሮፓ ውስጥ የሚታየው ብሔራዊ ጥቅምን ለማስከበር የሚደርገው ፉክክር በአውሮፓ ውስጥ አለመረጋጋት እንዲፈጠር አስተዋጾ ማድረጉም ተገልጹዋል።

በታላቋ ብርታኒያ ሊካሄድ የታሰበው እና ሀገሪቷ በአውሮፓ ሕብረት ሥር ትቀጥል ወይም አትቀጥል በሚል ሐሳብ የሚካሄደው የሕዝብ ውስኔ የአውሮፓን መከፋፈል የሚያባብስ እና አህጉራዊ ስሜትን አጥፍቶ በምትኩ ሀገርዊ ስሜቶች እንዲጎለብቱ የሚያደርግ ተግባር መሆኑም ተጠቅሱዋል።

በእዚህ ወሳኝ ጊዜ የቤተ ክርስቲያን ዋነኛው ተግባር ሊሆን የሚገባው አውሮፓ መለያ ባሕሪዋን መልሳ እንድትጎናጸፍ የሚያስችለውን መርሀ-ግብር መልሳ እንድታገኝ  ትንቢታዊ የተስፋ ድምፅ ማሰማት መሆኑም ተወስቱዋል። የአውሮፓ ብልጽግና እና መርሀ-ግብሮች ተግባራዊ ሊሆኑ የሚችሉት አውሮፓ አንድ ስትሆን ብቻ መሆኑም የአውሮፓ አብያተ ክርስቲያናት ሕብረት ጸሐፊ የሆኑ አባ ሄኪክሁቱኔን ገልጸዋል።

በጨረሻም የአውሮፓ ሕብረት የተመሰረተው መሰረታዊ የሆኑ የሰው ልጆች መብቶች እንዲጠበቁ፣ ነጻነት እንዲኖር፣ ዲሞክራሲ እንዲጎለበት እና እኩልነት እንዲኖር በሚያደርገው የሀገራት እና የሰዎች መብት ላይ የተመሰረተ እሴቶች ላይ በመሆኑ እነዚህን የአውሮፓ ሕብረትን ለመመስረት አስተዋጾ ያደርጉ እሴቶች በጋራ ማስከበር ከሁሉም እንደ ሚጠበቅ አሳስበው ለተግባራዊነቱም የአውሮፓ አብያተ ክርስቲያንት ሕብረት፣ የሲቪል ማሕበረሰብ እና የፖለቲካ ተቋማት ለአውሮፓ ግንባታ እና ሕብረት እንዲሁም ለአውሮፓ እና ለሰው ልጆች መልካምነት የበኩላቸውን ሊያበረክቱ ይገባል ማለታቸውም ተገልጹዋል።








All the contents on this site are copyrighted ©.