2015-06-03 16:30:00

ኡክራይን


የኤውሮጳ አገሮች የደህንነትና የትብብር ድርጅት፣ ሩሲያ ኡክራይንና በኡክራይን የሩሲያ ቋንቋ ተናጋሪው ክልል ከኡክራይን ለመገንጠል በሚል ዓላማ የሚንቀሳቀሰው ኃይል በጋራ በኡክራይን ክልል ተከስቶ ያለው ግጭት በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት በሚንስክ ሁለተኛ የሰላም ስምምነት ውል የሚጠራው ውሳኔ እግብር ላይ እንዴት ማዋል ለሚለው ጥያቄ መልስ ለማፈላለግ እ.ኤ.አ. ሰኔ 2 ቀን 2015 ዓ.ም. በበይሎሩሲያ ስብሰባ ማካሄዳቸው ተገለጠ።

በዶንባስ ክልል ተከስቶ ያለው ግጭት እልባታ እንዲያገኝ ታልሞ እ.ኤ.አ. መስከረም 2014 ዓ.ም. ቀጥሎም የካቲት 2015 ዓ.ም. የተደረሰው የቶክስ አቁም ስምምነት ሂደቱና ትግባሬው ምን እንደሚመስል በዚህ በበይሎሩሲያ ርእሰ ከተማ በመካሄድ ላይ ባለው ጉባኤ ውይይት ተደርጎበታል።

በስብሰባው የተሳተፉት የሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒ. በዶንባስ ክልል ተከስቶ ባለው ግጭት ሩሲያ የሩሲያ ቋንቋ ተናጋሪው ሰላማዊ ሕዝብ ለመከላከል ታጣቂውን ኃይል የመደገፍ መብትና ግዴታ አላት፣ አስፈላጊም ከሆነ በሩሲያው ሉአላዊው ክልልና አለ ዓለም አቀፍ ማኅበርሰብ ስምምነት የገዛ እራሷ ክልል ባደረገቸው በክሪመያም ጭምር የኑክሊየር ጦር መሣሪያ በተጠንቀቅ ለማቆም ግዴታና መብቱም አላት እንዳሉ ሲገለጥ፣ ይኽ በእንዲህ እንዳለም የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት በኡክራይን ምስራቃዊ ክልል ባለው ግጭት ሳቢያ ለሞት የሚዳረገው የክልሉ ነዋሪው ሕዝብ ብዛት ከፍ እያለ መምጣቱ ገልጦ በጠቅላላ እ.ኤ.አ. ከሚያዝያ 2014 ዓ.ም. ወዲህ 6 ሺሕ 4 መቶ ሰዎች መገደላቸው አስታውቋል።

የቶክስ አቁም ስምምነት በተለይ ደግሞ በዶነትስክና በሉጋንስክ ክልል ምንኛ ገቢራዊ እንደሆነ የፋሚሊያ ክርስቲያና መጽሔት ምክትል ዋና አዘጋጅ ፍላቪዮ ስካሊዮነ ከቫቲካን ረዲዮ ጋር ባካሄዱት ቃለ ምልልስ፦ የቶክሱ አቁም ስምምነት ጠቅለል ባለ አነጋገር ገቢራዊ ሆኗል ብሎ ለመናገር ይቻላል፣ ሆኖም ግን ግጭቱ በተቀጣጠለበት ክልል አሁንም መረጋጋት አይታይም። ምክንያቱን በሩሲያም ሆነ በኡክራይን ክልል ጠብ ለመጫር የሚቃጣቸው አሉ። ግጭቱ ክልላዊ ይምሰል እንጂ ዓለም አቀፋዊ መልክ ያለው ነው። ለሩሲያና ለኡክራይን ብቻ ሳይሆን ለሰሜን አትላንቲክ ቃል ኪዳን ጭምር አንገብጋቢ ክልል ነው። የተባበሩት የአመሪካ መንግሥታት ጥቅም ባጠቃላይ በዓለም የኃይል ምንጭ ንግድ ጥቅም አንጻር ሲታይ የሁሉም ጥቅም መስኅብ ክልል ነው ብለዋል።

ዶንባስ ለኡክራይን የኤኮኖሚ ጀርባ ነው። ስለዚህ ኡክራይን ጉዳዩ በቸልተኛነት እንደማትመለከተው የማይታበል ጉዳይ ነው። አለ ዶንባስ ኡክራይን በኤኮኖሚ አንጻር ብቻ ሳይሆን በመልክአ ምድር አቀማመጥ ጭምር ብዙ ትጎዳለች፣ ሩሲያ ካላት ፍላጎት አንጻር ወደ ኋላ እንደማትል የተረጋገጠም ነው። ለዚህም ነው ሩሱያ ለዚያ ክልል ልዩ የመሥተዳድር ሕግ እንዲኖረው ጥያቄ ያቀረበችው፣ ብለው ሆኖም ይኽ ሩስያ እምትጠይቀው ሕግ መመዘኛው ምንድር ነው? በኪየቭ አንጻር የዶንባስ ልአላዊነት ምን መልክ ይኖረዋል? ከሚሉት ጥያቄዎች አንጻር የሩስያው ጥያቄ ገቢራዊ ለማድረግ እጅግ አዳጋች ይሆናል በማለት ያካሄዱት ቃለ ምልልስ አጠቃለዋል።








All the contents on this site are copyrighted ©.